የ “ይቆጥቡ፤ ይሸለሙ!” መርሀ ግብር የህብረተሰቡን የቁጠባ ባህል እንዳበረታታ ተገለፀ፡፡

የ “ይቆጥቡ፤ ይሸለሙ!” መርሀ ግብር የህብረተሰቡን የቁጠባ ባህል እንዳበረታታ ተገለፀ፡፡ =========== ይህን የገለፁት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለ10ኛ ዙር ያዘጋጀውን “የይቆጥቡ፤ ይሸለሙ!” መርሀ ግብር ዕጣ የካቲት 25 ቀን 2014 ዓ.ም ባወጣበት ስነ-ስርአት ላይ የተገኙት የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ ናቸው፡፡ የሽልማት መርሀ-ግብሩ በ2004 ዓ.ም መጀመሩን ያስታወሱት አቶ አቤ፣ ለ10 ዙር ሲካሄድ በርካቶችን ቁጠባን ባህላቸው ማድረግ ከማስቻሉም በላይ የትልልቅ ሽልማቶች እድለኛም እንዳደረገ ገልፀዋል፡፡ ባንኩ የ“ይቆጥቡ፤ ይሸለሙ!” መርሀ ግብር በህብረተሰቡ የቁጠባ ባህል ላይ ያመጣውን ተጽእኖ ለመፈተሸ ጥናት ማስጠናቱን አቶ አቤ የገለጹ ሲሆን፣ የጥናቱ ውጤትም በመርሀ-ግብሩ ሳቢያ ብዙ ደንበኞች በመደበኛነት እንዲቆጥቡና ቁጠባቸውንም ለረጅም ጊዜ ሳያወጡ እንዲቆዩ እንዳስቻላቸው ማሳየቱን ተናግረዋል፡፡ “ቁጠባ እንደ ሀገርም ሆነ እንደግለሰብ ትልቅ ፋይዳ ያለው የብልሆች ምርጫ ነው” ያሉት አቶ አቤ፣ በኢኮኖሚ እድገታቸው ትልቅ ስፍራ የደረሱ ሀገራት ታሪክም ይሄንኑ እንደሚናገር አስረድተዋል፡፡ የሀገራችንን ልማት በአስተማማኝ ሁኔታ ለመደገፍ ከፍተኛ መጠን ያለው ሃብት ማሰባሰብ ከባንኩ እንደሚጠበቅ የገለጹት አቶ አቤ፣ የህብረተሰባችንን የቁጠባ ባህል በማበረታታት ይሄንኑ ለማሳካት ጥረት ይደረጋል ብለዋል፡፡ የጥናቱን ውጤት በመመርኮዝና አስፈላጊውን ማሻሻያ በማድረግ የሽልማት መርሀ-ግብሩ እንደሚቀጥል አቶ አቤ ተናግረው፣ ለ10ኛው ዙር ተሸላሚዎች የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት እንዲሁም መርሀ-ግብሩን በተሳካ ሁኔታ ለማከናወን ወሳኝ ሚና ለተጫወተው የብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ምስጋና አቅርበዋል፡፡ የካቲት 25 ቀን 2014 ዓ.ም በወጣው የ10ኛው ዙር የ“ይቆጥቡ፤ ይሸለሙ!” መርሀ ግብር ዕጣ 2 አፓርታማዎች፣ 10 አውቶሞቢሎች፣ 30 ባለ ሶሰት እግር ተሸከርካሪዎች እና 30 ላፕቶፕ ኮምፒውተሮች ለእድለኞች መድረሳቸው ይታወቃል፡፡ በዚህ መሠረት በ1ኛ ዕጣ በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኙ ሁለት ዘመናዊ አፓርታማ ቤቶች የሚያስገኙት የዕጣ ቁጥሮች 0275600863928 (አየር ጤና ቅርንጫፍ) እና 1188200154301 (ኦዳ ነቤ ቅርንጫፍ) በመሆን ወጥተዋል፡፡ የሁሉንም ሽልማቶች ዕድለኛ የዕጣ ቁጥሮች ቀጥሎ በተመለከተው ማስፈንጠሪያ (link) በመጠቀም ማየት ይቻላል፡፡ https://combanketh.et/cbeapi/uploads/10_fdfe62fa84.pdf